ለፍትህ አስተዳደሩ የሚደረገው ድጋፍ በበጎ ፈቃደኝነት ከሚደረጉ ተግባራት አንስቶ በህግ የታዘዙ ግዴታዎችን መፈፀም የሚያጠቃልል ሲሆን በህግ የተቀመጡ ግዴታዎችን ሣይፈፅሙ ሲቀሩ ግለሰቦችን በወንጀል ተጠያቂ የሚያደርጉ የወንጀል ድንጋጌዎች በወንጀል ህጉ ተደንግገዋል፡፡
በሃገራችን ህጎች መሰረት ህብረተሰቡ በ 3 መንገዶች በፍትህ አስተዳደሩ ተሳትፎ ወይም ድጋፍ ማድረግ ይችላሉ
ሀ) ወንጀል ተፈጽሞ ሲገኝ መረጃ ወይም ጥቆማ በመስጠት
ለ) ምስክር በመሆን
ሐ) ለፍርድ ቤቶች ተገቢው ክብር በመስጠት
ሀ) ወንጀል ተፈጽሞ ሲገኝ መረጃ ወይም ጥቆማ መስጠት
በወንጀለኛ መቅጫ ስነ-ስርዓት ህግ አንቀፅ 11 መሰረት ማንም ሰው ማንኛውንም ወንጀል ሲሰራ ያየ ወይም ያላየም ቢሆን የወንጀል ክስ እንዲቀርብ ወንጀሉን ለማስታወቅ መብት አለው በማለት ይደነግጋል፡፡ ሆኖም ግን ወንጀል የተፈጸመ መሆኑን ማሳወቅ ግዴታ የሚሆንበት ሁኔታዎች እንዳሉ በወንጀል ህጋችን በዝርዝር ተቀምጧል እነዚህም፡-
ከአንቀጽ 241-246 እና ከአንቀፅ 252-258 የተደነገጉትን ወንጀሎች ማለትም በአገሪቱ ህገ-መንግስታዊ ስርዓት፣ የፓለቲካና የግዛት ሉአላዊነት ፣የመከላከያ ሃይል ወይም የውስጥና የውጭ ደህንነት ላይ ወንጀል ሲፈጽም፣ ለመፈጸም ሲሞክር ወይም ሲዘጋጅ ያያ እንደሆነ ለሚመለከተው ባለስልጣን ማስታወቅ አለበት
በመከላከያ ሰራዊት እና በወታደራዊ ግዴታዎች ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን( ወታደራዊ ኩብላ ወይም ወታደራዊ አመፅ) የማሳወቅ ግዴታ
በሞት ወይም በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት የሚያስቀጣ ወንጀል መፈፀሙን ወይም የወንጀለኛውን ማንነት የማሳወቅ፣
እነዚህ ወንጀሎች መፈጸማቸውን ለሚመለከተው አካል አለማሳዎቅ የወንጀል ተጠያቂነት ወይም ቅጣት አለው፡፡
በሌላ በኩል ወንጀል ያጠቃላይ ህብረተሰቡን ሠላምና ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥል ተግባር እንደመሆኑ መጠን ወንጀልን መከላከልና ተፈፅሞ ሲገኝ ተጠርጣሪውን ወደ ፍትህ አደባበይ እንዲቀርብ ማድረግ የሁሉም ዜጋ ሃላፊነት ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል፡፡
ወንጀል መፈጸሙን ጥቆማ ለፓሊስ ከማቅረብ በተጨማሪ ማንኛውም ሰው የእጅ ከፈንጅ ወንጀል እየተፈጸመ ወይም ተፈፅሞ ካየ ተጠርጣሪውን ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በቁጥጥር ስር ማዋል እንደሚችል በወ/መ/ሥ/ሥ/ህግ አንቀፅ 50 ላይ ተደንግጓል፡፡ በዚህ አንቀፅ መሰረት ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ስር ለማዋል ሶስት መሰረታዊ ጉዳዮች መሟላት አለበት እነሱም፡-
ወንጀሉ እጅ ከፈንጅ የተፈፀመ መሆን አለበት
ወንጀሉ በግል አቤቱታ የሚያስቀጣ የወንጀል ዓይነት መሆን የለበትም
የተፈፀመው ወንጀል ከ3 ወር በላይ በፅኑ እስራት የሚያስቀጣ መሆን አለበት
ይህ ስልጣን ለግለሰቦች የተሰጠው ፓሊስ ወንጀል የተፈፀመበት ቦታ እስከሚደርስ ድረስ ወንጀለኞች ከአካባቢው እንዳይሰወሩ ለመከላከል ሲሆን ይህም በጊዜያዊነት የሚወሰድ እርምጃ ነው፡፡ በመሆኑም የተጠርጣሪውን ሰብዓዊ መብት በጠበቀ መልኩ በቁጥጥር ስር ካዋሉ በኋላ ለፓሊስ ማስረከብ ይገባል፡፡
ለ) ምስክር በመሆን ድጋፍ ማድረግ
በወንጀልም ሆነ በፍትሃብሄር ጉዳይ ላይ በፍርድ ቤት ክርክር እየተደረገበት ያለን ጉዳይ እልባት ለመስጠት በተከራካሪ ወገኖች መቅረብ ከሚገባቸው ነገሮች ውስጥ ጉዳዮን ያስረዱልኛል የሚሉዋቸውን የምስክሮች ስም ዝርዝር እና የሰነድ ማስረጃዎችን ከክሱ ወይም ከመልሳቸው ጋር አያይዘው ማቅረብ ይገባቸዋል፡፡
ምስክርነት ማለት ግለሰቦች በፍርድ ቤት በተያዘ በአንድ አከራካሪ ጉዳይ ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መልኩ የሚያውቁትን ነገር ፍርድ ቤት በአካል በመቅረብ የአስረጅነት ቃላቸውን የሚሰጡበት አግባብ ነው፡፡
አንድ ሰው ፍርድ ቤት በመቅረብ የሚሰጠው ምስክርነት በሁለት መልኩ ማየት እንችላለን፡-
መስክርነት መብት የሚሆንበት
ምስክርነት ግዴታ የሚሆንበት
ምስክርነት መብት የሚሆንበት አግባብ በፍርድ ቤት በተያዘ ጉዳይ ላይ የጉዳዮ ባለቤቶች( ከሳሽ ወይም ተከሳሽ) ጉዳያቸውን ለማስረዳት እራሳቸው ምስክር ሆነው ሲቀርቡ ነው፡፡
በሌላ በኩል ምስክርነት ግዴታ የሚሆንበት አግባብ ሲሆን ይህም ማለት በፍርድ ቤት የክርክር ሂደት ምስክር ሆኖ የተጠራው ግለሰብ ፍርድ ቤት ለመገኘት ፈቃደኛ ካልሆነ ፍርድ ቤቱ በተያዘው ጉዳይ ላይ ትክክለኛ ፍትሕ ለመስጠት ስለሚቸገር ግለሰቡ በፓሊስ ተገዶ እንዲቀርብ በማድረግ የምስክርነት ቃሉን የሚሰጥበት አግባብ በህግ ተደንግጓል፡፡
የፍርድ ቤት መጥሪያ ደርሶት ፍርድ ቤት ቀርቦ ለመመስከር ፍቃደኛ ያልሆነ ግለሰብ በወንጀል ህጉ በአንቀጽ 448 መሰረት የፍትህ እርዳታ መስጠትን እምቢ በማለት በሚል ርዕስ ሥር የወንጀል ተጠያቂነት ያስከትላል፡፡
“ፍርድ ቤት ወይም የዳኝነት ነክ ሥልጣን ያለው አካል በያዘው ጉዳይ ላይ በምስክርነት ወይም በልዮ አዋቂ ምስክርነት ወይም በአስተርጓሚነት እንዲረዳ በህግ መሰረት የተጠራ ማንም ሰው በቂ ምክንያት ሳይኖረው ሳይቀርብ የቀረ ወይም ለመቅረብ እምቢተኛ እንደሆነ ከሁለት ወር በማይበልጥቀላል እስራት ወይም ከአንድ ሺ ብር በማይበልጥ መቀጮ ይቀጣል በማለት ይደነግጋል፡፡”
ማንኛውም ሰው ፍርድ ቤት አከራካሪ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ሚያውቀውን ጉዳይ እንዲመሰክር የፍርድ ቤት መጥሪያ ሲደርሰው በመጥሪያው በተገለፀው ቀን እና ፍርድ ቤት በመቅረብ የምስክርነት ቃሉን በመስጥት የፍትህ አስተዳደሩን መደገፍ ይችላል፡፡
ሐ) ለፍርድ ቤቶች ተገቢው ክብር በመስጠት
በህገ-መንግስታችን የዳኝነት ስልጣን የተሰጠው ለፍርድ ቤቶች ብቻ ነው፡፡ ፍርድ ቤቶች የህግ የበላይነት መርህ ከማስከበር አንፃር ከፍተኛ ሃላፊነት የተጣለበት የፍትህ ተቋም በመሆኑ ማንኛውም ሰው ተገቢውን ክብር በመስጠት ድጋፍ ማድረግ ይገባል፡፡ ተገቢውን ክብር ለፍርድ ቤቶች መስጠት ይገባል ሲባል ፍርድ ቤቶች በህግ የተጣለባቸውን ሃላፊነት በሚወጡበት ወቅት ችሎት ማስቻያ ቦታዎች የዳኝነት ስራ መልካም አካሄድን ከሚያደናቀፍ፣ ከሚያውክ፣ ወይም የፍርድ ቤቱን ስልጣንና ክብር ዝቅ ከሚያደርጉ ተግባራት ነፃ መሆን ይገባቸዋል፡፡
አዲሱ የወንጀል ህጋችን በአንቀፅ 449 ማንም ሰው በፍ/ቤት ምርመራ ወይም የፍርድ ሥራ በሚከናወንበት ጊዜ ፍርድ ቤቱን ወይም የዳኝነት ሥራ በማከናወን ላይ ያለውን ዳኛ በማናቸውም መንገድ የሰደበ፣ ያወከ ወይም በነዚህ ላይ የዛተ እንደሆነ ከአንድ አመት በማይበልጥ ቀላል እስራት ወይም ከሦስት ሺ ብር በማይበልጥ መቀጮ ይቀጣል በማለት ይደነግጋል፡፡
ፍርድ ቤቱም የፍርድ ቤት መድፈር ወንጀል ተፈጽሟል ብሎ ካመነ ቀጠሮ ሳያደርግ ወዲያዉኑ በጥፋተኛው ላይ ቅጣት ሊወስን ይችላል፡፡
በአጠቃላይ ሕብረተሰባችን በወንጀል ወይም በፍትሃብሄር ፍትህ አስተዳደር ውስጥ በንቁ ሁኔታ በመሳተፍ የፍትህ አካላት የተቋቋሙበትን ዓላማ እንዲያሳኩ መርዳት ይገባዋል፡፡ እያንዳንዱ ግለሰብ ፍርድ ቤት ምስክር በመሆን፣ ወንጀል ተፈፅሞ ሲገኝ መረጃ ወይም ጥቆማ ለሚመለከተው አካል በመስጠት ወይም በህግ በተደነገገው አግባብ መሰረት ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ስር በማዋል እና ለፍርድ ቤቶች ተገቢውን ክብር በመስጠት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መልኩ በፍትህ አስተዳደሪ መሳተፍ ይችላል፡፡