የዕግድ ትዕዛዝ
ዕግድ በፍትሐብሔር ክርክሮች ላይ ራሱን ችሎ እንደ ውሳኔ ወይም በክርክሩ መሀል እንደ ጊዜያዊ ትዕዛዝ ይሰጣል፡፡ ዕግድ በውጤቱ ተከሳሹ ወይም ተጠሪው አንድ
ድርጊት ከመፈፀም እንዲታቀብ እንዲሁም የዕግዱ ትዕዛዝ አስገዳጅ ከሆነ አንድን ድርጊት በተወሰነ አይነት መንገድ እንዲፈጽም ያስገድደዋል፡፡
በኢትዮጵያ ከውል ውጭ በሚደርስ ኃላፊነት ሕግ ውስጥ የእግድ ትዕዛዝ የተፈፃሚነት ወሰኑ ተከሳሹ ጉዳት የሚያመጣ ነገር እንዳይሰራ በመስራት ላይ ቢገኝ እንዳይቀጥል ወይም እንደገና እንዳይጀመር ማገጃ እንጂ አንድ ተግባር እንዲፈጸም ማስገደጃ እንዳልሆነ ከፍ/ሕ/ቁ 2121(1) ድንጋጌ እንረዳለን፡፡ ዕግድ ማገጃ እና ማስገደጃ ትዕዛዛትን አጠቃሎ ሲይዝ ህገ ወጥ አስተዳደራዊ ተግባራትን ብቻ ሳይሆን በቸልተኝነት ግዴታን ባለመወጣት የሚፈፀሙ የአስተዳደር በደሎችን ለመቅረፍ የሚያስችል ውጤታማ መሳሪያ ነው፡፡
ተፈፃሚነቱ ደረቅና ፍፁም ሳይሆን ተስማሚ ባልሆኑ ሁኔታዎች ሁሉ ዳኛው ትዕዛዙን ላለመስጠት ሰፊ ስልጣን አለው፡፡ በፍትሐብሔር ሕጉ ቁጥር 2021/2/ እንደተመለከተው በሁለት ሁኔታዎች ትዕዛዙ ላይሰጥ ይችላል፡፡ ይኸውም ጥያቄ የተነሳበት ድርጊት በከሳሹ ላይ ጉዳት እንደሚያመጣ አሳማኝ ምክንያት ከሌለና እንዲሁም ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት ኪሳራውን በመክፈል ለመካስ ከተቻለ ፍርድ ቤት ዳኝነት ለመንፈግ ሰፊ ስልጣን አለው፡፡
የዕግድ ትዕዛዝ ራሱን የቻለ ውሳኔ እንደመሆኑ ክርክሩ ታይቶ ፍ/ቤቱ ውሳኔ ላይ ከመድረሱ በፊት ጊዜያዊ የዕግድ ትዕዛዝ በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 154 መሰረት ሊሰጥ ይችላል፡፡ ይህ በባህሪዩ ዘላቂ መፍትሄ ሳይሆን ውሳኔ እስከ ውሳኔ ቀን ሊደርስ የሚችልና የማይመለስ ጉዳት እንዳይደርስ በጊዜያዊነት የሚሰጥ ከለላ ነው፡፡ ትዕዛዙ የተላለፈለት ተከራካሪ ዕግዱን ባያከብር ድርጊቱ እንደ ፍርድ ቤት ንቀት ተቆጥሮ ቅጣት ይጣልበታል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በፍ/ሕ/ቁ 2121 መሰረት በቋሚነት የሚሰጥ የዕግድ ትዕዛዝ ተጨማሪ የአፈፃፀም ማመልከቻ ሳያስፈልግ ወዲያውኑ ተፈፃሚነት ሊኖረውና በተከሳሹ ሊከበር ይገባዋል፡፡ ይህ ባልሆነበት ጊዜ ፍ/ቤቱ በወንጀል ህጉ የተመለከተውን የፍርድ ቤት ንቀት ድንጋጌ በመጥቀስ ተገቢውን ቅጣት ይወስንበታል፡፡
የዕግድ ትዕዛዝ የሚጠይቅ አመልካች ወይም ከሳሽ በድርጊቱ ምክንያት በንብረቱ ወይም በመብቱ ላይ ቀጥተኛ ጉዳት እንደሚደርስበትና በጉዳዩ ጥቅም ያለው መሆኑን ማሳየት ይጠበቅበታል፡፡ ስለሆነም ድርጊቱ ከስልጣን በላይ ወይም አላግባብ በስልጣን መገልገል መሆኑ ብቻ በቂ አይደለም፡፡ በሌሎች አገሮች ግን ይህን የጠበቀ የከሳሽነት ብቃት (standing) በማላላት የተለየ ልዩ ጉዳት በአመልካቹ ላይ ባይደርስም ከማንም ሰው ጋር በሚጋራው ህዝባዊ መብቱ ላይ ጠቅላላ ጉዳት ሲደርስበት የዕግድ አቤቱታ የማቅረብ መብት ይኖረዋል፡፡





















































































































































































































